Friday, January 9, 2015

በልደቴ ቀን….


ዛሬ ኢየሱስ ተወልዷል፡፡ ልደቱን በሚገባ ላከብርለት እንደሚገባ እያንሰላሰልኩ ነው፡፡ ዛሬ ልዩ መሆን እንደሚገባኝም ይሰማኛል፡፡ የናርዶሱ ሽታ የናዝሪቱ ኢየሱስ…..የፍቅር አባት…..ዛሬ ምድርን እረገጣት፡፡ የምድር ላይ የመጀመሪያውን ሰከንዶች በለቅሶ ጀመረው፡፡ የሠላሙ አለቃ ሠላማችንን ሊሰጥ ለጥያቄያችን መልስ ይዞ በእናቱ እቅፍ ሆኖ እያለቀሰ ይህችን መራራ አለም ተቀላቀላት፡፡
     ጨቋኟ፣ቅብዝብዟ አለም አደቧን ልትገዛ ሰላሟን በበረት ተቀበለችው፡፡ ለሰላሟ ማረሻ የሚሆን ቦታ ጠፍቷት ስትባዝን ግርግም የነበረው ሠላሟ የከብቶችን ትንፋሽ ይሞቅ እንደነበር እንኳን ሳታስተውል ቀረች፡፡ ፍቅራችን ኢየሱስን ልታሞቀው በጨርቅ ጠቀለለችው…..የሠላም እናት የፍቅር መገኛ ንፁኋ ማሪያም፡፡ ደጉ ኢየሱስ አውን ምድር ላይ ነው፡፡ እንደሰው እንኖር ዘንድ፤ሰውን መሆን ሊያስተምረን ህፃኑ ግርግም ውስጥ ከከብቶች መሃል በጨርቅ ተጠቅልሎ ቅርጫት ውስጥ ተኝቷል፡፡ የአባቶች ምኞት፣የነቢያት ትንቢት፣የዳዊት የመዝሙሩ ቃና፣የስምኦን ናፍቆት መድሃኒት ዛሬ መጣልን፡፡
     ይህን በማውጠንጠን ላይ ሳለው የጓደኛዬ የእጅ ስልክ ያቃጭል ጀመር፡፡ አሳቤን ለሰከንዶች ገትቼ ዙሪያዬን እቃኝ ገባው፡፡ ሁሉም ውብ ነው፡፡ የሠላም ነፋስ፣የፍቅር ሙቀት፣የጠራ አየር….የአህዋፋት በረራ በራሱ ፍፁም ውበትን አይበት ጀመር፡፡ ከሩቅ የምሰማው የጉጉት ድምፅ ከዛፎቹ የአርምሞ እንቅስቃሴ ጋር ተደምሮ የማላውቀውን ዜማ ፈጥሮ ጭንቅላቴ ላይ ይጫወታል፡፡ ሙሉዋ ጨረቃ የዛሬውን ያህል አልደመቀችብኝም፡፡ ፀሐይዋን ለማሸነፍ ትግል ገጥማ የነበረችው ጨረቃ በሞት ሽረት ትግሉ የተሰነዘረባት የፀሐይ ጨረር ውበቷን ይበልጥ አፍክቷታል፡፡ እይታዬን የገታኝ ከፊት ለፊቴ የሚመጣው ሞርሳሳው ውሻ ነበር፡፡ ሞሪስ…የውሻው ስም ነው…አመጣጡ ለልፊያ እንደሆነ ያስታውቃል፡፡ ልብሴን እንዳያበላሽብኝ ፈንጠር ብዬ አስቀድሜ ተነሳው፡፡ እንደወትሮው ጭራውን ወደላይ አኮፍሶ ያርገበግበዋል…ደስ ብሎታል፡፡ የሞሪስን የደስታውን ምንጭ ባላውቅም ቅብጥብጡን ውሻ አይቼ ቀኑን አሰብኩት፡፡ ሃስብ ወደነበረው ወደቀደመ ሃሳቤ ተመለስኩ፡፡
ጠላታችንን እንወድ ዘንድ ያስተማረን ፍቅር የሆነው ኢየሱስ የተወለደበት ቀን፣የጨለማው ዘመን ማብቂያ የሆነው፣በትንሳዬውም የምህረት ቀን አንድ ብሎ የጀመረበት ኢየሱስ ዛሬ ተወልዷል፡፡ ሞሪስ ሳይቀር ለሰው ልጆች በመጣው በኢየሱስ የልደት ቀን ተደስቷል፡፡ ከሰዎች አልፎ ውሾችን ሊወድ የሚችል የሰው ስብህና ተፈጥሯልና….ለውሻ የሚሳሳ ሠው ተገኝቷል….በጨለማው ዘመን እንደነበረው የአዳኝ ላዳኝ ድራማ አክትሟል….የመስጠት ፍቅር በሰዎች ህሊና በቅሏል፡፡ ሰዎች እንዳይነጀሱ ይፀየፉት የነበሩት ዛሬ የሰዎች ልብ ፍርሃትን ሰብሮ በፍቅር ከውሻ ጋር መኖርን ጀምሯል፡፡ የዚህ መንፈስ ፈጣሪ፣ፍጥረትን የሚወደው መድህን ዛሬ ተወልዷል፡፡ ምድር ላይ ሊመላለስ በጨርቅ ተጠቅልሎ በፍጥረት ተከቦ ግርግም ተኝቷል፡፡
     ድንገት ከአፌ ቃል ይወጣ ጀመር፡፡ ‹‹ዛሬ ኢየሱስን እንዴት ላስደስተው?›› ለጓደኛዬ ነበር የጠየኩት፡፡ ለትንሽ ሰኮንዶች ዝምታ ሰፈነ፡፡ ‹‹ትህዛዙን ብትፈፅም የሚደሰትብህ ይመስለኛል፡፡›› አሪፍ ምክር ነበር፡፡ ትህዛዙን ግን ለማሰብ አልቻልኩም፡፡ ምን ነበር ትህዛዙ? ቀድሞ ዐይምሮዬ ላይ የመጣው ፍቅር ነበር፡፡ ፍቅር ብቻ! ምንአልባት ትህዛዙ ይሄ ከሆነ ልክ ነኝ ብዬ እራሴን ላሞግስ ጓደኛዬን አየሁት፡፡ ኢየሱስ ምድር ላይ ይመላለስ በነበረበት ጊዜ ያደረጋቸውም ያስተምራቸውም የነበሩት ነገሮች ከፍቅር የወጡ አልነበሩም፡፡ የሁሉም ነገር ማሰሪያው ፍቅር ነበር፡፡ አለምን የገዛ ገዥ የሆነው ታላቁ የፍቅር ሃይል….ይህ ሃይል ኢየሱስም ነበር፡፡ በዚህ ፍቅር ስትነደፍ ባልንጀራህን ትወዳለህ፣ጠላትህን የእልውናህ ማረጋገጫ የእውነትህ ማስረገጫ አርገህ ታፈቅረዋለህ፡፡ ያለምስጋና ትሰራለህ፡፡ ፍቅር ሲፈስብህ አዘንህ የአየር ያህል ይቀላል፡፡
     በመልሴ የረካ መሰለኝ ጭንቅላቱን እላይ ታች እየናጠ በፈገግታ ተመለከተኝ፡፡ ጓደኛዬ የገባውን ያብራራልኝ ጀመር…
‹‹በበረት መወለዱን አስበህ በረት ውስጥ መተኛት አይደለም ፍቅር…..አርያውን ተከትለህ አንተም አምላክ ትሆን ዘንድ፣የሰውን ልጅ ታፈቅር ዘንድ፣ሁሉን በመልካም እንድትከውን፤ደግነትን እንደ ገነት መግቢያ ትኬትህ አርገህ ሳታስብ የምታደርገው ስትሆን ያኔ የፍቅር ፀዳል ፊትህ ላይ ያበራል፡፡ፍቅር የተገለጠ ይሆናል፡፡ ኒርቫና!›› አሁን ንግግሩን እንዲያቆም ጣልቃ መግባት ነበረብኝ፡፡ ጓደኛዬ ቀላቅሎታል፡፡ ስለጌታ ፍቅር እየነገርኩት ኒርቫና ገለመሌ ቅብርጥርሶ ይለኛል፡፡ ንግግሩን ስለገታውበት ጓደኛዬ አልከፋውም ይልቅ ፊቱ ላይ ይበልጥ ፈገግታ ይነበብበታል፡፡ በራሴ አፈርኩ….ነገሮችን ቶሎ የምረዳ ልጅ መሆኔን ባውቅም እንዲ ችኮ መሆኔን ግን የጓደኛዬን ፊት አይቼ ተረዳውት፡፡ ማስቆም አልነበረብኝም….አሳቡን ሳይጨርስ በግታቴ ጨቋኝ አመለካከት ምን ያህል እንደተጠናወተኝ ገባኝ፡፡ ስለፍቅር እያወራን በፍቅር የሚነግረኝን መግታቴ አጢያት የፈፀምኩ ያህል ተሰማኝ፡፡ በበደለኝነት ስሜት ውስጥ ሆኜ ይቅርታ ለመጠየቅ ፈራ ተባ ስል አሳቢው ጓደኛዬ ያቋረጥኩበትን ወግ በሰፊው  ይተነትንልኝ ተያያዘው፡፡
ኢየሱስ ሁሌም እሱን እንመስል ዘንድ ሲወተውተን እንደነበር የሚያረጋግጥ የመፅሐፍ ቅዱስ ቃል አንስቶ ይሞግተኝ ጀመር፡፡ ኒርቫና የምንለው ፍፁም ሠው መሆንን፣የበራለት፣የተገለጠለት መሆኑን፤ኢየሱስም ፍፁም ሰው ለመሆኑ የተዋህዶን ምስጢር ይዘከዝከው ገባ፡፡ኢየሱስ የኖረውን ኑሮ ለመኖር እሱን መመሰል አለብን…ኢየሱስ የበራለት ነው፡፡ ይሄኔ ብልጭ አለብኝ፡፡ እንዴት የበራለት ነው ትለኛለህ? እሱ ራሱ ብርሃን ሆኖ ሳለ የበራለት ማለትህ አልተዋጠልኝም፡፡ ፈገግታው የማይለየው ጓደኛዬ እንዲህ ሲል አብራራልኝ…
‹‹ቡድሃ የበራለት ስለነበር የሱን ብርሃን የሚከተሉ አያሌ ተከታዮችን አፈራ…..ተከታዮቹ ቡድሃ በነቃበት፣በበራለት ገዥ አሳብ ተገዝተው የነቁ፣ያወቁ፣የበራላቸው ይሆኑ ዘንድ ዘወትር ቡድሃ በሄደበት መንገድ ይጓዛሉ፡፡ ስለቡድሃ ብዙ ተብሏል….ነገር ግን እንዴትም ብታወራው ሰው መሆኑን አትፍቀውም፡፡ እሱ እራሱን ስላወቀ ሌሎች እራሳቸውን ለማወቅ እራሱን ባወቀበት መንገድ ያም በጥልቀት ማሰብን ብቸኛው መንገዳቸው አደረጉት፡፡ ኢየሱስም ዩኒቨርስን የሚገዛውን የፍቅር ሃይል አስተዋወቀን፡፡ ፍፁም አምላክ ፍፁም ሰው ብንለውም በሰውነቱ ይህን ገዥ አሳብ ለአለም አስተዋውቋል፡፡ ምንም አርግ እንዴትም ሁን ከእርሱ አስተምህሮ ልትወጣ አትችልም፡፡ የእርሱ አስተምህሮ ሰውነት ነው፡፡ ሰው ሆኖ መኖርን….ፈጣሪን መምሰል አሳይቶናል፡፡ የእርሱ የፍቅር ጉልበት ሞትንም ድል ነስቷል….በሞት ላይ ጉልበት ሊኖረው የሚችለው ደግሞ ፈጣሪ ብቻ ነው….እሱም ፍቅር የሆነው ገዥ ሃይል ነው፡፡ ኢየሱስና ቡድሃ በዘመናት በታሪክም ወደዚህ ምድር የመጡበትም አላማ (በአይማኖት ድርሳኖች ላይ ሰፍሮ የምናገኘውን ማለት ነው) የተለያየ ቢሆንም የሄዱበት መንገድ ብዙዎችን አዋቂና የበራላቸው አድርጓቸዋል፡፡ ኢየሱስ የአስተምህሮቱ መጀመሪያም መጨረሻም ፍቅር በመሆኑ ተከታዮቹ በእርሱ መንገድ በመሄድ ልህለ ሰብ እስከመሆን በቁ፡፡ ተራራን ሲነቀንቁ፣ ባህር ላይ ሲራመዱ፣ደመና ጠቅሰው ሲሄዱ መስማት ጀመርን፡፡ እነሱ በእነሱ አልፈው የኒቨርስን ሆኑ፡፡ ሰላማቸው ከነሱ አልፎ ለሰው ዘር ሁሉ ሆነ፡፡ ያኔ ያልበራላቸው ጥላቻን ወለዱ፡፡ ማሳደድ፣ማሰር፣መግደል ጀመሩ፡፡ ለፍቅር ዋጋ የተከፈለበት መስቀል ለጦርነት አርማ ሆነ…የመስቀል ጦርነትም ምድርን በደም አጨቀያት፡፡ ያልበራላቸው በፍቅር ላይ ልዩነት ፈጥረው አለምን አከሰሏት፡፡ ፍቅርን በሚመቻቸው መንገድ እየተረጎሟት ጎራ ከፍሎ ቡድን መስርቶ የኔ በሚል መሻሉን በነፍጥ ሊያረጋግጥ ሰው አምላክ የሚሆንባትን የቀደመችውን ፍቅር አፈር ላይ ጣላት፡፤ አምላክ መሆኑ ቀርቶ የተረሳ በድን ሆነ፡፡ ሙሉዋ ፍቅር ዛሬ ብዙ ክፍልፋዮች ሆናለች፡፡ ለሞት ተላልፎ የተሰጠላት፤ዋጋ የተከፈለላት ፍቅር እንደያኔዎቹ የፍቅር ቤተሰቦች(የመጀመሪያ አማኞች) ትሆንላቸው እንደነበረች አይደለችም፡፡ ፍቅር አትነቅፍም ነበር…ዛሬ ቀንደኛ ተቺ ሆናለች፡፡ ያኔ ፍቅር አይለኛ ማግኔት ነበረች….መሳብ እንጂ ከቶውንም ገፊ አልነበረችም፡፡››
     የጓደኛዬ አሳብ ሳስብ የነበረውን የአይማኖት ልዩነት እና እንቶፈንቶውን ቁልጭ አድርጎልኛል፡፡ በአንዱ ዛፍ ብዙ ቅርንጫፎች ወተው በእኔ እሻል የቃላት ጦርነት ገጥመው ማየቱ ግንዱን ያለማስተዋል፤ወራጅ ውሃም ወደምንጩ እንደሆነ አለመረዳት ሆኗል፡፡
     ብቻ የዛሬውን ቀን ታሪክ ልሰራበት አስብያለው፡፡ ማሰብ ደግሞ መስራትን ይወልዳል፡፡ ምን ልስራ? እርግጥ ጓደኛዬ አፍቅር ብሎኛል፡፡ ባልንጀራዬን እንደራሴ ልወድ፣የሚረግሙኝን ልመርቅ…ሕይወቴን ዳጋመኛ ልውለደው፣የአዲሱ ሕይወቴም ልደት ከኢየሱስ ልደት ጋር ልዘክረው፡፡ከድርድር የነፃ ንፁህ ፍቅርን ለፍጥረታት ሁሉ ልስጥ፣ከዚህ አለም የቡድን ጦርነት ተለይቼ የሰላሜን አላቃ ላወድሰው….ፍቅሬ ከሰው አልፎ ተፈጥሮን ያስጎንብስ፡፡

                                     ቸር ይግጠመን!!!

No comments:

Post a Comment