Wednesday, November 13, 2013

ዳግማዊ ሠለሞን!

መቼም ስለ መርካቶ ያልተወራ ነገር ያለ አይመስለኝም….መርካቶን የማያውቃት ይኖራል ለማለትም አልደፍርም፡፡ ከአፍሪካ በስፋቱ ተወዳዳሪ ያልተገኘለት ትልቁ የገበያ ማህከል፡፡መርካቶ!
ስለ መርካቶ ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን በግጥም ‹‹አይ መርካቶ›› ተወዳጁ አብዱ ኪያር በዜማ ‹‹መርካቶ ሰፈሬ›› ና ወዘተ የብዙ የጥበብ ሰዎች እጅ ዳሷታል፡፡
እኔ የምለው መርካቶ ውስጥ ካሉ ቦታዎች አውቶብስ ተራ አካባቢ የሚገኘውን አዲስ ከተማ ት/ቤትን አስተውለውት ያውቃሉ?
የቀድሞ ልዑል መኮንን የአሁኑ አዲስ ከተማ መሠናዶ ት/ቤት የሠፈረበት አካካባቢ አስገራሚ ገፅታ ያለው ቦታ ነው፡፡ ት/ቤቱን ለተመለከተው እንዴት ሰው ሊማርበት ይችላል ብሎ ሊገረም እንደሚችል ጥርጥር የለኝም፡፡ እመኑኝ በድፍን ኢትዮጵያ እንደ አዲስ ከተማ አስገራሚ ት/ቤት አይኖርም፡፡
ቀን በእውቀት የታነፁ የአገር ተረካቢዎችን ለማፍራት የሚታትረው ት/ቤት ማታ ማታ በብዙ እንስቶች ተከቦ ይታያል፡፡
አንዳንዴ ዝም ብዬ ስመለከተው ጠቢቡ ሰለሞንን የሆነ ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም ሁለቱም በሴት የመታጀባቸው ጉዳይ ነው፡፡
የዘመኑ ሰለሞን አዲስ ከተማ አመሻሽ ላይ ልጅነታቸውን ባልጨረሱ ወጣት ሴቶች ተከቦ ማየቱ የተለመደ ነው፡፡
እዚህ ጋር ጥበብና ሴት ያላቸውን ግንኙነት እንድናስተውል ይጋብዘናል…ሁለቱም የሆነ አይነት ዝምድና ያላቸው ይመስላል፡፡ የሚገርመው ምንም እንኳን ት/ቤቱ በአስቸጋሪ አካባቢ ላይ ቢገኝም ለዘመናት በእውቀት አሰጣጡ ተስተካካይ ማጣቱ ደግሞ ይበልጥ አግራሞታችንን ይጨምረዋል፡፡
ዘፋኙ ‹‹ የምንነጋገርበት ቋንቋው አንድ አይነት 
        አዲስ ከተማ ነው የተማርንበት››
አንድ ሠሞን ት/ቤቱ ይነሳል ተብሎ በነበረበት ወቅት ‹‹መርካቶ ምድር ገንዘብ እንጂ እውቀት ምን ሊረባ›› ብለው የሚያስቡ ቱባ የመርካቶ ባለሀብቶች ትልቅ የገበያ ማዕከል ለማድረግ ቢቋምጡም ዳግማዊ ሠለሞንን ማን ደፍሮት ከነክብሩ ቀን በተማሪዎች ማታ በእንስቶች ተከቦ ዘላለማዊነቱን እያሳበቀ ዘሬም ድረስ አለ፡፡ ማታ ላይ የት/ቤቱ ደጃፍ በታዋቂ የአገራችን ሰዎች በተዋቡ ጋዜጣና በፅሔቶች  ምንጣፍ ወለሉን ሸፍነው የንባብን ጥማት ሊቆርጡ ይታትራሉ፡፡ እንቡጥ እንስቶች ደግሞ አጥሩን በመውረር ሴትነታቸውን ለገበያ የሚያቀርቡበት ልዩ መድረክ ነው፡፡ የቀኑ ያ የእውቀት አውድማ አመሻሹ ላይ የወሲብ መናኽሪያ ይቀየርና ት/ቤት ደርሶ የማያውቅ እግር ሁላ በስሜት እየተነዳ አዲስ ከተማ ት/ቤት ከቸች ይላል፡፡ ት/ቤቱ በራፍ ላይ በትልቁ ‹‹ ኑ ብርሃንን ተቀበሉ ሂዱናም አንፀባርቁ›› የሚለውን ጥቅስ  ለተማሪዎች በመተው ‹‹ ኑ የጭኔን በረከት ተቀበሉ ሂዱናም ዝናዬን አውሩ›› በመል ተቀይሮ ሌቱ ቀን ይሆናል፡፡ በመርካቶ ፀሐይ አትጠልቅም ያለው ማን ነበር? ሠላም ባልትና ወይስ አዲስ ከተማ ት/ቤት?
ዙሪያው በማህበራዊ ቀውሶች የተከበበው ይህ ት/ቤት ግቢው እጅግ በስነ ምግባር የታነፁ ጠማሪዎች ያሉበትና ውጤታማ የሆነ ለመሆኑ ምስክር አያሻንም፡፡
ከፖሊስ ጋር አይጥና ድመት  ሆነው ስራቸውን የሚሰሩት እንስቶች አንዳንዴ የፖሊስ ደረቅ ጎማ መቅመስ የግድ ይላቸዋል፡፡ ምክንያቱም ከት/ቤቱ ፊት ለፊት የሚገኘው ጠባብ ቅያስ በሕጋዊ ሴተኛ አዳሪዎች የተሞላ ስለሆነ እኚህ አጥር ጥግ ሞገደኛውን ወንድ የሚጠባበቁ እንስቶች ሕገ-ወጥ ተብለው መሆኑ ነው….እኒህ ሁሉ በዳግማዊ ሰለሞን የየእለት ተግባራት ናቸው፡፡
መርካቶ!!


No comments:

Post a Comment