Sunday, April 14, 2013

አበሻ ኩሩ ነው!?

የትኛው አበሻ? የድሮው ወይስ የአሁኑ? እውን በምናችን ይሆን እንዲ አበሻ ኩሩ ነው በሚል ብሂል ውጥርጥር ያልነው፡፡ ቲሸርቶቻችን የሚናገሩት ስለኩሩነታችን፤ስለጀግንነታችንና ስለብዝሃነታችን ከሆነ ሰንበትበት ብሏል፡፡ኩሩ ማህበረሰብ ለራሱ የተለየ ቦታ ያለውና ሌሎች ላይ የማይደርስ በሎሎች የተከበረ ለመሆኑም የማህበረሰብ ሳይንስ ሊቃውንት የሚስማሙበት አቅ ነው፡፡
የአበሻ ኩሩነት እንደቻይናውያን እንቁራሪት አለመብላቱና ምግብ መምረጡ ከሆነ ኩሩነት ትርጉሙ መቀየር አለበት ባይ ነኝ፡፡ ኩሩነታችን አለመንበርከካችንና በነጭ አለመገዛታችን  ነው የምንል ከሆነ ደግሞ ለዚህ ዘመን አበሾች የማይመጥን ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ነጮች እንደዋዛ ክብራችንን ከነጠቁን ዘመናት አለፉ....በቱሪስት መዳረሻ በሆኑ ከተሞቻችን  ኩሩው አበሻ ለፈረንጆች የሚያሳየውን ፍቅር ስንመለከት ሰውኛ የሆነ የጨዋ ሕዝብ ልዩ ምልክት መሆኑን እንታዘብና ወደራሳችን ተመልሰን ጓዳችንን ስናይ የሰውኛ ባህሪ መሆኑ ይጠፋብንና አድር ባይነታችን ይጎላብናል፡፡ ሴቶቻችን የአበሻ ወንድ በአፍንጫዬ ካሉም ሰንበትበት ብለዋል...ቄሶቻችን በቤተ እምነት መዘክር ውስጥ ‹‹ፈረንጅ መቷል ውጡ›› ማለት ከጀመሩም አመታት አለፉ፡፡ ማለፍ ክልክል ነው፤መንገዱ ዝግ ነው በሚባሉ ቦታዎች ላይ አበሾች ተኮልኩለው ነጭ እንደዋዛ ሲያልፍና ፍቃድ ሲሰጠው ስናይ ልማታዊነታችን ታውሶን በቸልታ የምናልፈው የእለት ተእለት ተራ ጉዳይ ከሆነም ሰንብቷል፡፡ ኩሩነት በአባቶች ታሪክ መታበይ ከሆነ እውነት ኩሩ አለመሆናችንን ላስረግጥ እወዳለው፡፡
የአበሻ ኩሩነት በጎዳና የወደቀውን ወንድሙን የሚያንቋሽሽና አለውልህ ከማለት የኘጮችን በጎነት የሚናፍቅ እከሌ እኮ እስፖንሰር አግኝቶ....የምንል የጉድ ልጆች ከንቱ ኩራት... ሲረግጡን የምንረገጥ የራሳችን ማንነት የጠፋብን ተአምር ጠባቂዎች፤የምላስ ቁማርተኞች፤ሆዳችን ክብራችን የሆነ ዘመነኛ ኩሩዎች!
ወዳጄ ኩሩ ነኝ ብለህ ታስባለህ? እንግዲያውስ ለራስህ ቦታ ይኑርህ፤እራስህን አክብር፤ በቆዳ ልዩነት የማታምን ቅድሚያ ለኢትዮጵያዊው ወንድሜ የሚል አትዮጵያዊ ብሔርተኛ ሁን!!
በዚህ ርዕሰ ጉዳይ ላይ ወደፊት በሰፊው እናወጋለን፡፡