Sunday, February 10, 2013

ሃ/ማርያም ሆይ ጫማው ሰፍቶዎታል!!!

ሃ/ማርያም ሆይ ጫማው ሰፍቶዎታል!!!

የሠዎች አስተሳሰብ በኖሩበት ማህበረሰብ እንዲሁም በግለሰባዊ ማንነት ላይ ተመርኩዞ የተለያየ እንደሚሆን እሙን
ነው፡፡ከአንድ ማህፀን በወጡ ሁለት መንትያ ልጆች መካከል እንኳን የሚኖረው የአስተሳሰብ ልዩነት ስንመለከት ሠዎች
በየትኛውም መለከኪያ ተመሳሳይ የሆነ የአስተሳሰብ ደረጃ ሊኖራቸው እንደማይችል እንረዳለን፡፡ በአንድ ነገር ላይ
ተመሳሳይ አቋም ቢኖረንም ነገሩን የምንረዳበት መንገድና የአፈፃፀሙ ሁኔታ ከሰው ሰው ተለያይቶም እንመለከታለን፡፡
የአብዮታዊ ዲሞክራሲ ልሂቃን የሆኑት መሪዎቻችን በአንድ ልብ እናስብ በአንድ ቃል እናውራ ብለው መነሳታቸው
ምናልባትም በመንፈሳዊ ሕይወታችን የምናውቃቸው የቤተክርስቲያን ሊቃውንት ሰልስቱ ምዕት እንደ አንድ ልብ አሳቢ
እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ በመሆን በቤተክርስቲያን ላይ ክህደት የፈፀሙትን ሰዎች አውግዘው እንደነበር ድርሳናት
ያወሱትን እንድናስታውስ ይጋብዘናል፡፡ መቼም መለኮታዊ ሃይል ካልዳሰሰን በቀር ሠዎች በአመለካከትና በአነጋገር
ፍፁም አንድ ሆነው ያለአሳብ ልዩነት ነገሮችን ሊወስኑ እንደማይችሉ በቤተሰብ ውስጥ በሚወሰኑ ውሳኔዎች እንኳን
መታዘብ እንችላለን፡፡(ፈላጭ ቆራጭ አባወራ ካልሆነ፡፡)
ላለፉት 20 እና 21 አመታት ውስጥ በኢትዮጵያ ፓርላማ ውስጥ ነገሮች ሲወሰኑ መለኮታዊ ሃይል የዳሰሳቸው ይመስል
ያለ አንዳች ክርክርና ተቃውሞ ውሳኔዎች ሲወሰኑ አይተናል፡፡መቼም ያለአሳብ ልዩነት ጥሩ ነገር ማግኘት አይቻልም
እንዲሁም የተሻለውን መወሰን ፍፁም ከባድ መሆኑንና ተከትሎት የሚመጣውም ውጤት አስደሳች እንደማይሆን መረዳቱ
አስቸጋሪ አይሆንም፡፡ አምባ ገነኖች ለሚያነሱት አሳብ ተቃውሞን እንደማይሹ የፓርላማ ውስጥ ሽሙጥና ዘለፋ ምስክር
ነው፡፡በአለም ላይ ስልጣን የያዙ አምባገነን መሪዎች ሁሉ ተመሳሳይ የሚያደርጋቸው ባህሪ ቢኖር ለሕብረተሰቡ
እናውቅልሃለን፤እኛ ከሌለን…የሚሉ ፈሊጦችን በአደባባይ መፎከር ነው፡፡አብዮታዊ መሪዎቻችን ቢሆኑም ለኢትዮጵያውያን
እናውቅልሃለን ከማለት ውጭ ፍላጎታችንን ጠይቀውን አያውቁም፡፡በየቀበሌው የሚደረገው ሕብረተሰባዊ ተሳትፎ
የሚያሰፈልገው ስብሰባም ቢሆን ፖለቲካዊ ፋይዳው እንጂ ለህብረተሰቡ የሚያስገኘው አንዳችም ኢኮኖሚያዊም ይሁን
ማህበራዊ ጥቅም እንደሌለ ኑሮዋችን በቂ ምስክር ነው፡፡
የሆነው ሆኖ መጤው ጠ/ሚንስትር የቀድሞውን ጠ/ሚንስትር ጫማ በማጥለቅ የግል ባህሪያቸውንና ውስጣቸው የተደበቀውን
ሃይል እያጠፉ ያለ ይመስለኛል፡፡ ሠው እንደራሱ እንጂ እንደጎረቤቱ አይኖርም የሚለው ኢትዮጵያዊው ብሂል እዚህ
ጋር ወሃ ቋጥሮ እናገኘዋለን፡፡አቶ ሃ/ማሪያም እንደራሳቸው እንጂ እንደ አቶ መለስ ሊመሩን ከቶውንም አይገባም፡፡
እንደሚታወቀው የአቶ መለስ ጥንካሬ ፓርቲያቸውን ጠንካራ ከማድረግ አልፎ የሚኒሊክን ቤተ መንግስት የግላቸው
እስከማድረግ አድርሷቸዋል፡፡ ደግም ይሁን ክፉ በታጋዩ ፈርሆን የግል አመለካከትና ጥንካሬ አገሪቷ ላይ ለ21
አመት  ያሻቸውን ሲፈፅሙ እንደነበር የወራት ትዝታችን መሆኑን ከሞቱ በኋላ በትግል ጓዶቻቸው
ተመስክሮላቸዋል፡፡አቶ መለስ ከአልባኒያን ስርዓት እስከ ልማታዊ መንግስትነት ያደረሳቸው የራሳቸው የግል
አመለካከትን በለሌች ላይ በተለይ በትግል ጓዶቻቸው ላይ የማሳረፍ ታለቅ ተሰጥሆ ስለነበራቸው ነው፡፡(የአብዮታዊ
ዲሞክራሲ ልሂቃን ትግላቸው የአልባኒያ አይነት ስርዓት በኢትዮጵያ ለማምጣት እንደነበር የምንዘነጋው
አይደለም፡፡የሚገርመው ነገር መገንባት የሚፈልጉት ስርሃት ጨቋኝ በሚባለው መንግስቱ እንኳን የማይደገፍ መሆኑ
ነው፡፡በወቅቱ አልባኒያ በሆጃዎች ትመራ የነበር ፍፁም አምባ ገነንነት የሰፈነባት አገር ነበረች፡፡)